ወያኔ ትግሬዎች በሸዋ ሮቢት ከተማ የ85 አመት መነክሴን አስገድደው ደፈሩ!!

"አሁንማ ምንኩስናዬም ፈረሰ፤ አረከሰኝ”  በአሸባሪው የተደፈሩት የ85 አመቷ መነኩሴ - ሸዋሮቢት
*********************
Ethiopian Press Agency /የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት/
Dec 13 2021
(ኢ ፕ ድ)

እማሆይ ዛሬ የምንኩስና ቆባቸውን አውልቀው ጥቁር ሻሽ ጸጉራቸው ላይ ጣል አድርገዋል። የምንኩስናው ክብር፣ ስለ ሰማያዊው አለም የተውት ስጋቸው በጉልበተኞች ረክሶ ነፍሳቸውን አቆሽሾታልና የምንኩስና ምልክታቸውን አውልቀዉ ዘመድ እንደሞተበት ሰው ጥቁር ሻሽ አስረዋል።

አሸባሪው የህወሓት ወራሪ ቡድን ሸዋሮቢት ከተማ መግባቱን ተከትሎ በተፈጸመባቸው በደል “እረክሻለሁ፣ ስጋዬም ነፍሴም ቆሽሿል” ይላሉ።

በሸዋሮቢት ከተማ የቀበሌ 02 ነዋሪ የሆኑት እማሆይ በላይነሽ (ስማቸው የተቀየረ) 10 ልጆችን ወልደው የሳሙ  የ85 ዓመት የእድሜ ባለፀጋ ናቸው።
እርሳቸው እንደተናገሩት፤ የአሸባሪው ህወሓት ታጣቂዎች ከተማዋን ተቆጣጥረው በነበረበት ወቅት የእለት ጸሎታቸውን አድርሰው ሰላም አሳድረኝ ብለው በተኙበት እኩለ ሌሊት በራቸው በድንገት ተንኳኳ። 


"...ውድቅት ሌሊት ላይ በሬ  ተንኳኳ። ማነህ ስለው? ክፈቺ አለኝ። ድምጹ የልጄን ድምጽ መሰለኝና ከፈትኩኝ። ሲገባ የማላውቀው ሰው ነው። እንደገባም ለምን ቶሎ አልከፈትሽም በማለት ደጋግሞ በጥፊ መታኝ።  ወደቅኩ። በወደቅኩበት ጭንቅላቴን፣ ሆዴን ደጋግሞ ረገጠኝ።እባክህ ተወኝ፣ እናት የለህም በእናትህ ይሁንብህ እያልኩ ቢያዝንና ቢተወኝ ብዬ በወደኩበት ሆኜ ለመንኩት። እሱ ግን እንኳንስ ሊያዝንልኝ  'ሴትና ወንድ እንሁን' አለኝ። ተጫወተብኝ።  እጄንም እንደምታዩት አድርጎ ደብድቦ አቆሰለኝ። አረከሰኝ” ሲሉ እያነቡ ነገሩን።

በሸዋሮቢት ተግኝተው እማሆይን ያነጋገሯቸው የኢፕድ ዘጋቢዎች እንዳረጋገጡት፤ እማሆይ ለመቆምም ለመንቀሳቀስም አቅም አጥተዋል። እንደልብ ለመንቀሳቀስ ጉልበታቸው አልፈቅድላቸው ብሏል። ተገደው መደፈራቸው ብዙ ደም እንዲፈሳቸው አድርጓል። ከህሊና ህመሙ ባይብስባቸውም ዛሬም የእጃቸው እና የሰውነታቸው ቁስል ክፉኛ ህመም ላይ እንደጣላቸው ነግረውናል።

“...ያ ሰው መሳይ አውሬ አርክሶኝ ሄደ፤ በማግስቱ ሙሉ ቀን ከማህጸኔ ደም ሲፈሰኝ ዋለ። አካላቴ ሁሉ ደቋል፤ የሰውነቴ ህመም አሁንም ድረስ አለ" ያሉት እማሆይ በላይነሽ፤ ወገባቸውን እንደሚያማቸው፣ ሽንታቸውን ሲሸኑ ፊኛቸውና ማህጸናቸው አካባቢ ህመም እንደሚሰማቸው ገልጸውልናል። ቆመው ለመራመድ መቸገራቸውንና በሰው ድጋፍ እንደሚንቀሳቀሱም ዘጋቢዎቻችን ተመልክተዋል።

እስካሁን ህክምና እንዳላገኙ የጠቆሙት እማሆይ፤ "እዚህ ያደረሰኝ ፈጣሪ ለወደፊቱም እርሱ ያውቃል" ሲሉም ሲቃ እየተናነቃቸው የሚያሳስባቸውን የነፍሳቸውን መንገድ ነግረውናል።
 
"አሁንማ ምንኩስናዬም ፈረሷል፤ አረከሰኝ፤ እንግዲህ ለነፍስ አባቴ ተናግሬ፣  እንደህጻን  ዳግም ክርስትና መነሳትና ንስሃ መግባት አለብኝ" ብለውናል።
ከአማራ ህዝብ ጋር ሂሳብ ሊወራርድ ኢትዮጵያን ሊያፈርስ ወረራ የፈጸመው የአሸባሪው ህወሓት ቡድን በአማራ እና አፋር ህዝቦች ላይ ወረራ ከፈጸመ በኋላ ሊታሰቡ እንኳን የሚከብዱ በደሎችን ፈጽሟል።

በቅርቡ የኢፕድ ዘጋቢዎች በሰሩት ሌላ ዘገባ በሰሜን ሸዋ በቡድን የተደፈሩ አዛውን እናቶች መኖራቸውን እና ከእናቶች አንዷም የልጃቸውን አይን ላለማየት ራሳቸውን ማጥፋታቸውን መዘገባችን የሚታወስ ነው።

በዘላለም ግዛው (ሸዋሮቢት)


   




0/Post a Comment/Comments